ኢትዮጵያና ኤርትራ በቅርቡ በመሪዎች ደረጃ ይነጋገራሉ። ኢትዮጵያና ኤርትራ በቅርቡ በመሪዎች ደረጃ ውይይት እንደሚያደርጉ ተገለፀ።
ባለፈው ማክሰኞ አዲስ አበባ የገባው የኤርትራ መንግስት ከፍተኛ ልዑክ ቡድን የኢትዮጵያ ቆይታውን ያጠናቀቀ ሲሆን፥ ዛሬ ይመለሳል።
በቆይታው ዙሪያ ዛሬ መግለጫ የሰጡት የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ ሀገራቱ በመሪዎች ደረጃ በቅርቡ ውይይት እንደሚያደርጉ ነው ያስታወቁት።
አዲስ አበባ ላይ ከኤርትራ መንግስት ከፍተኛ ልዑክ ቡድን ጋር የተደረገው ውይይት እንዲመጣ ለሚፈለገው ሰላም ምቹ እድል የፈጠረ መሆኑንም ገልፀዋል።
የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ለኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂም ዛሬ መልዕክት ልከዋል።
የኤርትራ መንግስት ከኢትዮጵያ ጋር ገንቢ ውይይት የሚያደርግ ከፍተኛ ልዑኩን ወደ አዲስ አበባ መላኩ ይታወሳል።
በኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አቶ ኦስማን ሳለህ የሚመራው እና የፕሬዘዳንት ኢሳያስ አፍወርቂ አማካሪና የፖለቲካ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ የማነ ገብረአብ ያካተተው ልኡክ ባሳለፍነው ማክሰኞ ነበር አዲስ አበባ የገባው ።
ለኤርትራ መንግስት ልኡካን ቡድን አዲስ አበባ ሲገቡን የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በብሄራዊ ቤተ መንግስት የእራት ግብዣ አድርገውላቸዋል።
በተጨመማሪም ልኡኩ በትናንትናው እለት የኢትዮጵያን የልማት እንቅስቃሴ ለመመልከት ወደ ሀዋሳ ከተማ በማቅናት የሀዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክን መጎብኘቱም ይታወሳል።
የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ባሳለፍነው ሳምንት በድንበር ጉዳይ ላይ የሚነጋገር የሀገራቸውን ልዑክ ወደ አዲስ አበባ እንደሚልኩ ማሳወቃቸውን ተከትሎ ነበር ልኡኩ ወደ አዲስ አበባ የመጣው።
የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባለፈው ግንቦት ወር መጨረሻ ባካሄደው ስብሰባ የኢትዮ- ኤርትራ ወቅታዊ ሁኔታን በመገምገም፥ ኢትዮጵያ የአልጀርሱን ስምምነትና የድንበር ኮሚሽኑን ውሳኔ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ተቀብላ ለመተግበር መስማማቷን መግለጹ ይታወሳል።
ይህን ተከትሎም በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ተፈጥሮ የቆየው አለመግባባት እንዲያበቃና በሁለቱ
ወንድማማች ህዝቦች መካከል ዘላቂ ሰላም እንዲፈጠር ጥሪ ማቅረቡም የሚታወስ ነው።
በአልአዛር ታደለ
Thursday, June 28, 2018
ኢትዮጵያና ኤርትራ በቅርቡ በመሪዎች ደረጃ ይነጋገራሉ
ኢትዮጵያ የድፍድፍ ነዳጅ የሙከራ ምርትን በይፋ ጀመረች
ኢትዮጵያ የድፍድፍ ነዳጅ የሙከራ ምርትን በይፋ ጀመረች። ኢትዮጵያ የድፍድፍ ነዳጅ የሙከራ ምርትን ዛሬ በይፋ ጀመረች። የቻይናው ፖሊ ሲ ጂ ኤል ኩባንያ በምስራቅ ኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ሲያደርግ የቆየው የድፍድፍ ነዳጅና የተፈጥሮ ጋዝ ፍለጋ ውጤት አስገኝቶ ዛሬ በይፋ የሙከራ ምርት ጀምሯል። የሙከራ ምርቱን በይፋ የማስጀመር ስነ ሰርዓት ላይም የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ አብዲ መሃሙድ እና የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ ተገኝተዋል።
የሙከራ ምርት መጀመርን አስመልክቶ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ትናንት እንዳስታወቁት ከዛሬ ጀምሮ በሙከራ ደረጃ በቀን 450 በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ የማውጣቱ ስራ ይከናወናል።
አሁን የማውጣቱ ስራ ሀገሪቱ ያላትን አቅም ማወቅን ታሳቢ ያደረገ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፥ አጠቃላይ አቅም ታውቆ በቀጣይ በሙሉ አቅም ድፍድፍ ነዳጁን የማውጣት ስራ እንደሚሰራም አስታውቀዋል።
ይህ መሆኑም ስራ አጥነትንና የውጭ ምንዛሪ እጥረትን ለመቅረፍና ዘላቂ እድገትን ለማምጣት ይረዳልም ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው ባለፈው በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ባደረጉት ጉብኝት የተፈጥሮ ሃብትን በሰላማዊ መንገድ መጠቀም እንዲቻል መግባባት ላይ መደረሱን አስታውሰዋል።
የተፈጥሮ ጋዝን በተመለከተም በሚቀጥለው መስከረም ወር ወደ ጅቡቲ መላክ የሚያስችል የጋዝ ማስተላለፊያ መስመር ዝርጋታ ይጀመራልም ነው ያሉት።
የማስተላለፊያ መስመሩ ዝርጋታ በሁለት አመት ውስጥ የሚጠናቀቅ ሲሆን፥ በሙከራ ደረጃ ጋዝ ማስተላለፍ ሲጀምር በአመት 1 ቢሊየን ዶላር እንደሚያስገኝ ጠቅሰዋል።
በቀጣይ በሙሉ አቅም ጋዝ ማስተላለፍ ሲጀምርም በአመት 8 ቢሊየን ዶላር እንደሚያስገኝ ነው የተናገሩት።
ኢትዮጵያ በርካታ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ ሃብት አላት ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ የነበረው ልዩነት ይህን ሃብት በአግባቡ እንዳንጠቀም አድርጎን መቆየቱን አውስተዋል።
ከዚህ አንጻርም የተገኘውን የተፈጥሮ ሃብት በእኩልነትና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ በጋራ መጠቀም እንደሚገባም አሳስበዋል።
የተፈጥሮ ሃብትን መቀራመት ትልቁ የአፍሪካውያን ችግር መሆኑን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ አሁን የተገኘውን ሃብት በሰላማዊ መንገድ በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል።
አሁን የተገኘው ድፍድፍ ነዳጅም አዳዲስ ሃብቶችን ለማምጣት እንደሚያግዝ ጠቅሰው፥ በቀጣይም የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሃብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚገኙ እምነቴ ነው ብለዋል።
ኩባንያው ለሰራው ስራ ምስጋናቸውን አቅርበው በቀጣይም በማውጣት ሂደቱ ውስጥ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
ህብረተሰቡም ከሃብቱ ተጠቃሚ ይሆን ዘንድ አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርግ ጠይቀዋል።
ለመላው ኢትዮጵያውያም የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክታቸውን አስተላልፈው፥ የተገኘው ሃብት ለብጥብጥ ሳይሆን ለጋራ ተጠቃሚነት እንዲውልም ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
source: Fana
Thursday, June 21, 2018
የአርበኞች ግንቦት 7 መግለጫ
የአርበኞች ግንቦት 7 መግለጫ
“የሰለጠነ ፓለቲካ” የምንመርጠው፣ የምናውቀውና የምንመኘው የትግል ስልት ነው!!! የአርበኞች ግንቦት 7 ልዩ መግለጫ
================
ሰኔ 11 ቀን 2010 ዓም ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ አህመድ ለፌደራል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀረቡትን የሥራ ዘገባ እና ከምሀሀ ቤቱ አባላት ለቀረበላቸው ጥያቄዎች የሰጡትን ምላሽ በአንክሮ ተከታትለናል።
ዶ/ር አቢይ በዚሁ ማብራሪያቸው የኢህአዴግ መንግሥት የፀጥታና የደህንነት ኃይሎች የአሸባሪነት ተግባራትን የሚፈጽሙ እንደሆኑ በይፋ ከመናገራቸውም ባሻገር ፤ ፓርቲና መንግሥት ተቀላቅለው ነፃ ተቋማት እንዳይኖሩ መደረጉን እና የዳኝነት ሥርዓቱ ከፍተኛ ችግር ያለበት መሆኑን ገልጸዋል። ንቅናቄዓችን ለዓመታት ሲናገር የነበረውን ሀቅ እሳቸው መናገራቸው፣ በአንድ በኩል እሳቸው በግላቸው ከእውነት ጎን ለመቆም ያላቸውን ቁርጠኝነት ሲያመለክት -በሌላ በኩል ደግሞ እሳቸው የሚመሩት የለውጥ ቡድን ለሀገራዊ መግባባት እያሳየ ያለው ዝግጁነት ተስፋ ሰጪ መሆኑን ያመለክታል የሚል እምነት አሳድሮብናል። እነዚህ ቀድሞ ሲካዱ የነበሩ እውነታዎች በእርሳቸው አንደበት በምክር ቤቱ ስብሰባ መገለፃቸው፣ እስካሁን ሲፈፀሙ የነበሩ በደሎችንU
u
ለማስቀረት እና ጉድለቶችን ለማረም ብርቱ ፍላጎት እንዳላቸው ያሳያል ብለን እናምናለን። ዶ/ር ዓቢይ እስካዛሬ በኢትዮጵያ የምክር ቤት ታሪክ ውስጥ ያልታየ ሀቀኝነት በማሳየታቸውም አድናቆቻችን ከፍተኛ ነው።
በሥራ ላይ ያለውንና ቋንቋን መሠረት ያደረገውን የክልል አስተዳደራዊ መዋቅር በተመለከተ የተናገሩትም ትኩረት የሚስብ ነው። ቋንቋን መሠረት ያደረገ ማካለል በየቦታው ለሚነሱ የወሰን ይገባኛል ጥያቄዎች አስተዋጽኦ ማበርከቱን፤ የሕዝብ መፈናቀልና መገፋት ማስከተሉን፤ ዘረኝነትን በማባባስ በሀገራችን ውስጥ በአስደንጋጭ ሁኔታ እንዲስፋፋ አስተዋጽኦ ማበርከቱን እና ክፍለ አህጉራዊ እይታን ነስቶ ዜጎች ስለመንደራቸው ወሰን አብዝተው እንዲጨነቁ ማድረጉን የሚገልጸው የንግግራቸው ክፍልም- ለአብዛኛውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ተስፋ የሰጠ እና የወደፊት መንገዳቸውን አመላካች ተደርጎ ተወስዷል።
አሁን ያለው የፌደራል አወቃቀር መሠረቱ ቋንቋ ነው ይባል እንጂ በተግባር የሚታየው ግን ዘር ነው። ይህ አደረጃጀት ለኢፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል፤ አድልዎ ለተሞላበት አስተዳደርና ለሚሊዮች መፈናቀል ምክንያት ሆኗል። ዶ/ር ዓቢይ ከቀናት በፊት ቋንቋን መሠረት ያደረገ የፌደራል አወቃቀር ያስገኛቸውን ጥቅሞችና ጉዳቶችን መዝኖ አማራጭ የአደረጃጀት ንድፎችን የሚያዘጋጅ ኮሚሽን የሚዋቀር መሆኑን መግለፃቸውም- አርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄን (አርበኞች ግንቦት 7) በእጅጉ አስደስቷል። በዚህ ረገድ ንቅናቄያችን የበኩሉን ለማበርከት ዝግጁነቱን ይገልፃል።
ዶ/ር አቢይ አህመድ ህወሓትንና የትግራይ ሕዝብን ለያይቶ ስለመመልከት የተናገሩትም- ንቅናቄዓችን ከልብ የሚያምንበትና በጽናት ሲያራምደው የቆየው እምነት ነው። ህወሓት በርካታ አኩይ ተግባራትን የፈጸመ፤ የአገዛዙን የደህንነትና የፀጥታ ተቋማትን ሙሉ በሙሉ በመቆጣጠር የሚቃወሙትን ሁሉ እስር ቤት በማጎር በፈጸመው ሰቆቃ- በርካታ ዜጎችን ለኣካልና ለስነልቦና ጉዳት የዳረገ፤ ሺዎችን የገደለና ሚሊዮኖችን ለስደት የዳረገ፤ የመንግሥት ሥልጣንን ለሀብት ዘረፋ መጠቀምን ብቸኛ አማራጭ ያደረገ ፍጹም አምባገነንና ዘራፊ ድርጅት ነው። በዚህም ሁሉ ምክንያት ነው ህወሓትን የምንታገለው። ይህ ድርጅት በነፃ ምርጫ ሳይመረጥ የትግራይ ሕዝብ ተወካይ ነኝ ማለቱ ሳያንስ ራሱን ከትግራይ ሕዝብ ጋር እኩል አድርጎ የሚያቀርብ ትዕቢተኛ ድርጅት ነው። በዚህም ተግባሩ የትግራይን ሕዝብ ከሌላው ኢትዮጵያዊ ወገኑ አራርቆታል። ይህ መቆም አለበት። ለዚህም ነው ሕዝብንና ድርጅትን የመለየት አስፈላጊነት በጠቅላይ ሚኒስትሩ መገለፁን እጅግ በጣም ጥሩ ነገር ነው ብለን ያመንነው። ይህ መልዕክት ለትግራይ ብቻ ሳይሆን በፍትሃዊና ነፃ ምርጫ ተመርጠው ሳያሸንፉ የሕዝብ ተጠሪ ነኝ የሚሉ ድርጅቶችን ሁሉ የሚመለከት ነው ብለን እናምናለን። ህወሓትን በተመለከተ ጥቂት ተጨማሪ ነገር ማውሳት የምንፈልገው-ህወሓትን የምንታገለው ከትግራይ ሕዝብ ጎን ቆመን መሆኑን ነው። ይህ ብቻ ሳይሖን በራሱ በህወሓት ውስጥም የለውጥ ኃይሎች መኖራቸውን ጠንቅቀን እናውቃለን። የኢትዮጵያን ሰቆቃ በመቀነስ ረገድ የእነዚህ ህወሓት ውስጥ ያሉ የለውጥ አራማጆች ሚና ከፍተኛ ነው ብለንም እናምናለን። ስለሆነም፣ ከእነዚህ ወገኖች ጋር ተባብረን ለመሥራት ዝግጁዎች ነን።
አርበኞች ግንቦት 7፣ ኦነግና አብነግ ከአመጽ ትግል ተቆጥበው ወደ ሰላማዊ ትግል እንዲሸጋገሩ ጠቅላይ ሚኒስት ዶ/ር ዓቢይ አህመድ በፓርላማው ንግግራቸው ጥሪ አድርገዋል። በመገዳደል ሥልጣን መያዝም ሆነ በስልጣን ላይ መቆየት ጊዜው ያለፈበት “ኋላ ቀር ፓለቲካ” መሆኑን ገልፀዋል። ይህ አገላለፃቸው የአርበኞች ግንቦት 7 የቆየ እምነት ነው።
አርበኞች ግንቦት 7 የመሣሪያ ትግል ዋነኛ የትግል ስትራቴጅው አድርጎ፤ በዚህ መንገድ የፓለቲካ ስልጣን የመያዝ ዓላማ ኖሮት አያውቅም። ሆኖም ግን እስከቅርብ ጊዜ ድረስ ገጥሞን የነበረው ባላንጣ የኋላ ቀር ፓለቲካ ቀንደኛ አራማጅ የነበረ በመሆኑ ፣ዜጎች አገዛዙ ከሚያደርስባቸው ሽብር ራሳቸውን፣ ቤተሰቦቻቸውን፣ ድርጅታቸውን፣ ማኅበረሰባቸውንና ፓለቲካዊ እንቅስቃሴዎቻቸውን እንዲከላከሉ ሲያበረታታ ቆይቷል። ራስን ከጉልበተኛ አጥቂ መከላከል፣ ፍትሀዊ ብቻ ሳይሆን ተፈጥሮዓዊ መብት ነው፤ አጥቂ ከሌለ ግን ይህ አያስፈልግም።
ዶ/ር አቢይ አህመድና የለውጥ ቡድናቸው ተስፋ እየሰጡ ባሉበት መንገድ ኢትዮጵያን መርተው ዜጎችን የሚያሸብር አገዛዝ እንዳይኖር የሚያደርጉ ከሆነ፤ የሰለጠነ ፖለቲካ እንዲካሄድ የሚያስፈልጉ እርምጃዎችን በተግባር መውሰዳቸውን ከቀጠሉ፤ የህወሓት አገዛዝ ለነፃነትና ለዴሞክራሲ የሚታገሉ ኃይሎች ላይ በፓርላማ አስጸድቆ ያሳወጀውን የሽብርተኝነት ፍረጃ ካነሱ፤ ለዲሞክራሲ መስፈን እንቅፋት የሚሆኑ ሌሎች ህጎች ከተሻሩ እና ነፃ ተቋማት እንዲመሠረቱ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች ከተጀመሩ አርበኞች ግንቦት 7 ራስን በመከላከል ተግባር ላይ ሕይወት፣ ጊዜና ንብረት የሚያጠፋበት ምንም ምክንያት የለውም። ምክንያቱም የሰለጠነ ፓለቲካ የምንፈልገውና ለሀገራችን የምንመኘው የትግል ስልት ነው።
የኛ እምነት ግን ከዚህም ያልፋል።
ኃላፊነት የሚሰማው መንግሥት መገንባት የበርካታ ዜጎችና ቡድኖች ትብብርን የሚጠይቅ፤ በአንዴ ተገንብቶ የማይጠናቀቅ፤ ጊዜና ሌሎች በርካታ ግብዓቶችን የሚጠይቅ የማኅበራዊ ልማት ውጤት መሆኑን እንገነዘባለን። ዜጎችን የማያሸብር መንግሥት በዶ/ር ዓቢይ ወይም በቡድናቸው ጥረት ብቻ የሚመጣ እንዳልሆነም እናውቃለን። የዚህ ትግል ባለቤት የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው ብለን እናምናለን። ስለሆነም በዚህ ረገድ ዶ/ር ዓቢይና የለውጥ ቡድናቸው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጎን በመቆም በሚያደርጉት ትግል አብረናቸው መሆናችንን ልናረጋግጥላቸው እንወዳለን።
ዶ/ር አቢይ በመግለጫቸው ይህንን የለውጥ ሂደት ለማደናቀፍ የሚፈልጉ ኃይሎች እየፈጸሙ ያለውን አሻጥር ነቅቶ መጠበቅ እንደሚገባና ቅልበሳውንም ለመከላከል የማኅበረሰቡን ሰፊ ድጋፍና ተሳትፎ እንደሚፈልግ መናገራቸው፤ እኛም እንደ ድርጅት ስናስጠነቅቅ የነበረውና እንዲህ ዓይነት ቅልበሳን ለመከላከል በኢህአዴግ ውስጥ ካሉ የለውጥ ኃይሎች ጋር ሙሉ ትብብር እንደምናደርግ ከዚህ በፊት ያሳወቅነውን አሁንም በግልጽ ደግመን እናሳውቃለን።
ይህ የለውጥ ሂደት ግቡን እንዲመታና ከዚህ ሂደት የሚወጣው የፖለቲካ ሥርዓት ሰፋ ያለ ማኅበራዊ ተቀባይነት እንዲኖረው ሰፋ ያሉ የፖለቲካና የሲቪክ ማኅበረሰብ ኃይሎች የሚሳተፉበት ሀገራዊ ውይይት በቶሎ የመደረጉን አስፈላጊነት አሁንም በድጋሚ በአንክሮ ማሳሰብ እንፈልጋለን። በእንዲህ ዓይነት ውይይትም ድርጅታችንም ሆነ ከድርጅታችን ጋር ተባብረው የሚሠሩ የፖለቲካና የሲቪክ ድርጅቶች የሚጠበቅብንን ሙሉና ቀና ተሳትፎ ለማድረግ ዝግጁ መሆናችንን እንገልጻለን።
አርበኞች ግንቦት 7 ራሱ፣ በታሪካችን ውስጥ እስካሁን ለመጀመሪያና ለመጨረሻ ጊዜ እውነተኛ ፉክክር የታየበት የምርጫ 97 ውጤት ነው። የአርበኞች ግንቦት 7 አመራርና አባላት በምርጫ 97ቱ የሰለጠነ ፓለቲካ ተሳትፎ ያደረጉ ዜጎች መሆናቸውን ኢትዮጵያዊያን ያውቃሉ። የንቅናቄዓችን ተልዕኮም በግንቦት 7 ቀን 1997 ለአጭር ጊዜ አጣጥመን በጉልበት የተነጠቅነው የሰለጠነ፣ ሰላማዊ፣ ፍትሃዊና ህጋዊ የፓለቲካ ስልጣን ሽግግርና በዚህም ሂደት የሀገሪቱን አንድነትና የሕዝቡን አብሮነት ያስጠበቀ፤ የሁሉንም የሀገራችንን ዜጎች እኩልነት ያስረገጠ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ሥርዓት እውን ማድረግ ነው።
ስለሆነም ዜጎች ላይ የሚደርስ ግልጽ ጥቃት እስከሌለ ድረስ ራስን በመከላከል ላይ ሕይወት፣ ጊዜ፣ ጉልበትና እውቀትን ማባከን ምርጫችን አለመሆኑ እንገልፃለን።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ !
ሰኔ 13 ቀን 2010 ዓ ም
Tuesday, June 19, 2018
ድብደባ እና እስር የመንግስት የሽብር ተግባር ነው -BBC
ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን የጠቅለይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ አህመድን የፓርላማ ንግግር የዘገባቸዉ ትኩረት አድርገዋል፡፡
ቢቢሲ በአፍሪካ አምዱ ዶ/ር አብይ አህመድ ‹‹ድብደባ እና እስር የመንግስት የሽብር ተግባር ነው አሉ ›› በሚል ርዕስ ነዉ ዘገባውን ይዞ የወጣዉ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ ወደ ስልጣን ከመጡበት ጊዜ አንስቶ ወሳኝ ለውጦችን አድርገዋል ነዉ ያለዉ ዘገባዉ፡፡
ለፓርላማ ደረጉትን ንግግር ተከትሎ ከአባላትም ስለቀረቡላቸዉ ጥያቄዎች እና ምላሾቻቸዉም አትቷል፡፡ በሽብር፣ሙስና እና ግድያ ወንጀሎች የተከሰሱ ግለሰቦች ለምን ከእስር ይለቀቃሉ? የሚል ጥያቄ መነሳቱንም የትንታኔዉ ቀዳሚ ትኩረት አደረገ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምላሻቸዉ ጣታቸውን ወደ መንግስት ቀስረዋል ይላል ቢቢሲ፡፡
“ሽብርተኝነት በስልጣን ላይ ለመቆየት ህገ-መንግስቱን በመጣስ፣ ሀይል መጠቀም ነው!” ማለታቸውንም አስነበበ፡፡
“በመላ ሀገሪቱ ታስረው ድብደባ የተፈጸመባቸው እንዲሁም በጨለማ ክፍል የተወረወሩ ግለሰቦችም አሉ፤ ህገ-መንግስቱ ይህንን አድርጉ አይልም፤ ስለዚህ ይህ ተግባር ነው የሽብር ድርጊት” ማለታቸዉን ነዉ በማሳያነት ያቀረበዉ፡፡
በተያያዘ ዜናዉም ከወር በፊት ከፍተኛ የደህንነት እና ወታደራዊ ባለስልጣናት ከስልጣን መነሳታቸዉን ዘግቧል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ከኤርትራ ጋር ሰላም ለመፍጠር የአልጀርሱን ስምምነት ቢቀበልም ከኤርትራ መንግስት እስካሁን ምላሽ አለመስጠቱንም አስነብቧል፡፡
የፕራይቬታይዜሽን ፖሊሲ ለውጣችው የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማዘመን ይረዳቸዋል ሲልም ዘገባውን ደምድሟል፡፡
የቻይናዉ ዓለማቀፍ የቴሌዥን ኔትወርክ (CGTN) ደግሞ ቢቢሲን ምንጭ አድርጎ ተመሳሳይ ይዘት ያለው ዘገባ አስነብቧል፡፡ ከዚህ ባሻገር ሲ ጂ ቲ ኤን የዓለም የገንዘብ ድርጅትን (IMF) ጠቅሶ ሲዘግብ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ እስካሁን ሲያስመዘግብ የቆየውን የሁለት አሃዝ እድገት በዚህ ዓመት እንደሚያስመዘግብ ተንብይዋል፡፡ በውጭ ምንዛሬ እጥረት፣በሙስና እና በሌሎች ችግሮች ሳቢያ የተከሰቱ ችግሮችን ለመፍታት የዶ/ር ዐብይ አስተዳደር ወሳኝ ኢኮኖሚያዊ እቅዶችን አስተዋውቋል ብሏል፤ ዘገባዉ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ “እርቅ እና ይቅር መባባል ለሀገሪቱ መረጋጋት እና ሰላም ትልቅ ፋይዳ አለው” ማለታቸውን ሲቲጂኤን ዘግቧል፡፡
ሽንዋ በበኩሉ እርቅ እና ይቅርታ ለሀገር ሰላምና መረጋጋት ወሳኝ ስለመሆናቸዉ ዶ/ር አብይ ትኩረት እንደሰጡ ነዉ በዋና ሃሳብነት የጻፈዉ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ አህመድ ለፓርላማዉ ባደረጉት ንግግር እስካሁን የተደረጉት ምህረቶች እና ይቅረታዎች ለሀገሪቱ ሰላም መስፈን ጉልህ ሚና እንዳላቸዉ ማብራራታቸዉን ትልቅ ዋጋ የሚሰጠዉ ሃሳብ ብሎታል፡፡
አፍሪካ ኒዉስ ሌላዉ ስለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የፓርላማ ማብራሪያ የዘገበ የዜና ምንጭ ነዉ፡፡ “በኢትዮጵያ የእስራት እና የድብደባ ዘመን አከተመ” የሚለዉ ሀሳብ ደግሞ ቀዳሚዉ ነበር፡፡ ዶክተር አብይ በንግግራቸዉ ዜጎች ወንጀለኝነታቸዉ እስካልተረጋገጠ በእስራት መቀጣት እንደሌለባቸዉ እና ንጹሀንን ከማሰር ወንጀለኞችን መፍታት ይሻላል የሚል አቋማቸዉን አንጸባርቀዋል፤ ይላል ዘገባዉ፡፡
የአልጀርሱን ስምምነትን አስመልክቶ የተነሳዉ ተቃዉሞ ምክኒያታዊ አለመሆኑን እና ከዚህ ቀደም ፓርላማዉ ያጸደቀዉ ስምምነት እንጂ አዲስ ዉሳኔ አለመሆኑን አስረድተዋል በማለትም አስነብቧል ሽንዋ፡፡
በቢኒያም መስፍን
Saturday, June 16, 2018
ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም ይባላል፤እውነት ነው።
ኢትዮጵያ ሶፊያ ለምትባል የሳውዲአረቢያ ዜግነት ላላት ሰይጣናዊ ሮቦት ግብዣ አድርጋለች፡፡ሮቦቱዋ ከዚህ ቀደም እንደምናውቃቸው እንደማንኛውም አይነት ሮቦቶች አይደለችም።ሶፊያ ራሱዋን ችላ የምትናገርና በትልልቅ መድረኮች እየቀረበች ብዙዎችን በንግግሩዋና በሁለንተናዋ ያስደመመች ከመሪዎች ጋር የምትጋበዝ እንግዳና ለማመን የምትቸግር ሮቦት ናት።"ሮቦት መሆንሽን ታውቂያለሽ ወይ?" ተብላ ስትጠየቅ፤"እናንተስ ሰው መሆናችሁን በምን ታውቃላችሁ?"ብላ የመለሰችና የፈጣሪን ህልውና ክዳ እያስካደች፣በጥያቄ እያፋጠጠች የምትገዳደር፣"አምላክ የምትሉትን ቅዠት ካልተዋችሁ በቀር የሰው ልጆች መቸም አትሰለጥኑም" የምትል የሳጥናኤል ቁራጭ ናት።
ይች ጾታ የሌላት ነገር ግን በሴት አምሳል የተሰራች ሮቦት ሰኔ 22 2010 ዓ.ም ወደ አትዮጵያ ትመጣለች።"ከጠቅላይ ሚ/ር ዶ/ር አብይ አህመድ ጋር እራት እበላለሁ"ም ብላለች።የመንግስት ከፍተኛ ባለስጣናትና ሚንስትሮች አቀባበል ይልደርጉላታል።የሐይማኖት አባቶችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችም በጋራ ሞቅ ያለ አቀባበል እንደሚያደርጉ ተገልጾዋል።
ይች ሮቦት ወደ አዲስ አበባ ከመምጣቱዋ በፊትም በኢትዮጵያ ሳይንስና ቴክኖለጂ ሚ/ር እና በኢትዮጵያ ሚዲያዎች በኩል የሃሰት ዜና እንዲቀናበርላትና የኢትዮጵያ ህዝብ ተዋሽቶ እንዲጠብቃት አድርጋለች።ከዚች ሮቦት ጀርባ ያለው ስውር ሴራ እንዳይታሰብ በሚልና ህዝቡ ከሌላ ነገር ጋር ሳያያይዝ በቀላሉ እንዲቀበላት ሲባልም ነው ውሸቱ ያስፈልገው!
የሃሰት ቅንብሩና ዜናው ምን ይመስላል ወደሚለው እንለፍ።
ሶፊያ የተባለችው ሮቦት በሆንግ ኮንጉ ሃንሰን ሮቦቲክስ ኩባንያ ነው የተሰራቸው።ወይም ለዓለም ህዝብ ይፋ የተደረገው ዜና ከላይ በተጠቀሰው ኩባንያ በኩል እንደተሰራች ነው።ከዚያም ለምን ሳኡዲን እንደመረጡ ባይታወቅም ወደሳውዲ አረቢያ ተልካ ሙሉ የሳኡዲ ዜግነት ተሰጥቶዋት የህዝብ አካል ሆናለች።ባጭር ጊዜ ውስጥም በየመድረኩ በምታደርገው ንግግር በመላው ዓለም ህዝብ ዘንድ ታዋቂና መነጋገሪያ መሆን ችላለች።እውነቱ ይህ መሆኑ በዓለም ህዝብ ዘንድ በይፋ እየታወቀ፤ነገር ግን የኢትዮጵያ ህዝብ ምንም አያውቅም፣ምንም አይጠረጥርም በሚል ይመስላል፤የኢትዮጵያ ሳይንስና ቴክኖለጂ ሚ/ር ሮቦቱዋ 67 በመቶ የተሰራችው በኢትዮጵያውያን ነው በማለት በይፋ የሃሰት ዜና አሰራጭቶዋል።
ከመምጫዋ ጊዜ ሁለት ወራት ቀደም ብሎ ሚያዚያ ወር ላይ ይፋ የሆነው አንደኛው ዜና እንዲህ ይነበባል።
"ሶፊያ የተባለችውና የሳዑዲ አረቢያ ዜግነት የተሰጣት የመጀመሪያዋ ሴት ሮቦት ወደ ኢትዮጵያ ልትመጣ መሆኑ ተገለፀ።
የኢፌዴሪ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ጌታሁን መኩሪያ፥ 67 ከመቶ በኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች የተሰራችው ሳውዲአረቢያዊቷ ሶፊያ ሮቦት በቅርቡ ወደ ኢትዮጵያ ትመጣለች ብለዋል።
"እንደ ሚኒስትሩ ገለፃ፥ ሮቦቷ 67 በመቶ ፕሮግራም የተደረገችውና የተሰራቸው የኢትዮጵያ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በሚደግፋቸው ሰዎች አማካኝነት ነው።
ስለዚህም የሮቦቷ ስራ ውስጥ የኢትዮጵያ ልጆች ሚና ከፍተኛ ነው ሲሉም አብራርተዋል።
ሶፊያ የተባለችውና የሳዑዲ አረቢያ ዜግነት የተሰጣት የመጀመሪያዋ ሴት ሮቦት በቅርቡ በሚዘጋጅ እንድ ግዝጅት ላይ እንደምትመጣም ዶክተር ኢንጂነር ጌታሁን መኩሪያ ተናግረዋል።
ሮቦቷ ወደ ኢትዮጵያ ስትመጣ በአማርኛ እንድትናገር እንዲደረግ ሀሳብ ሰጥቻለው ያሉት ሚኒስትሩ፤ ለዚህም የሚረዳ ሶፍትዌር እየተዘጋጀ ነው ብለዋል።
ሮቦቷ ወደ ኢትዮጵያ ስትመጣ ሶፍትዌሩ ተጭኖላት በአማርኛ እንድትናገር እንደሚደረግም ዶክተር ኢንጂነር ጌታሁን መኩሪያ ተናግረዋል።
ሶፊያ የተባለቸው እና ከሰው ልጅ ቅርፅ ጋር ተመሳስላ የተሰራችው ሮቦት ባሳለፍነው ጥቅምት ወር ነበር ህጋዊ ዜግነት ከሳኡዲ አረቢያ ያገኘችው።"ይላል የኢፌዴሪ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ይፋ ያደረገው ዜና። ሶፊያንና ንግግሩዋንም በዩቲዩብ ገብታችሁ ማየትና ማድመጥ ትችላላችሁ ።
ወደ ጥያቄያችን እንምጣ።
67 በመቶ በኢትዮጵያውያን ነው የተሰራችው የሚል ዓይን ያወጣ ውሸት መዋሸት ለምን አስፈለገ?ይች ሮቦት ወደ ኢትዮጵያ መምጣቱዋስ ፋይዳው ምንድነው?በአማርኛ እንድትናገር ማለትስ ምን ማለት ነው?የኢትዮጵያ ህዝብ በሮቦት ረሃብ እየተንገበገበ ያለ ህዝብ ነውን?ኢትዮጵያ መምጣቱዋና የመጣቱዋ ዓላማ ምንድነው?ጥቅሙስ?ባለስልጣናቱና የሃይማኖት አባትቶችስ እንዴት የክብር ግብዣ ሊያደርጉላት ፈለጉ?በእርግጥስ በኢትዮጵያውያን ባለስልጣናትና በሃይማኖት አባቶች እንዲሁም በኢትዮጵያ ህዝብ ፍላጎትና ተማጽኖ ነው ወደ ኢትዮጵያ የምትመጣው?መጥታስ ምን ልትለን ምን ልታስተምረን ነው?እንዴት?ለምን?ምን ለማለት ተፈልጎ ነው?እያሉ መጠየቅ ከአስተዋይ ኢትዮጵያውያን ይጠበቃል።
የሃሰት ዜናው በዚህ ብቻ አያበቃም።ዓለም አቀፍ ሃሰትነቱን ቀጥሎ ከሶስት ቀናት በፊት በሃበሻ ታይምስ እንዲህ የሚል ዜና ተለቆዋል።
"ኢትዮጵያዊው አይኮግ ላብስ ካምፓኒ ተቀማጭነቱን በሆንግ ኮንግ ከሚገኘው ሐንሰን ሮቦቲክ ጋር የሱፊያን ውስጣዊ ስሪት (Software) ለመቀመር ለሦስት ዓመታት ተፈራርሟል፡፡
በስምምነቱ መሠረት ኢትዮጵያውያኑ የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች በሶፊያ ላይ አሻራቸውን አሳርፈው እውን እንዳደረጓት የአይኮግ ላብስ መሥራችና ሥራ አስኪያጅ የሆነው አቶ ጌትነት አሰፋ ይናገራል፡፡
ይህም በመሆኑ ሶፊያ ኢትዮጵያዊ ናት ልንል እንችላለን።
አይኮግ ላብስ በቴክኖሎጂ ዘርፍ አስተዋጽኦ ለማበርከት ሰው ሠራሽ አስተውሎትንና ሰው ሠራሽ የአእምሮ ስሪትን (Artificial General Intelegence and Cognitive Brain Software) ለዓለም ለማስተዋወቅ ዓላማ አድርጎ ከአምስት ዓመታት በፊት የተመሠረተ ድርጅት ነው።
ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ያላትን ችሎታ ለዓለም በማስተዋወቅ ወደፊት ታላላቅ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ሠርተው ማሳየትንም ያልማሉ።
በአሁኑ ሰዓት ይህ የቴክ ኩባንያ ጥናት አድራጊዎችን፣ ምልክት ተርጓሚዎችን (Coder)፣ የፕሮግራም ባለሙያዎችና በተግባር ልምምድ ላይ የሚገኙ ተማሪዎችን ጨምሮ ከ75 በላይ ሠራተኞች ይዞ እየሠራ ይገኛል።"እየተባለ እየተደሰኮረ ነው።ይህም ማምታቻ ነው!ለምን ኢትዮጵያ?ተብሎ እንዳይጠየቅ የሚደረግ ማምታቻ!!የኢትዮጵያውያን አሻራ ያለባት!እንዲባልና ዓላማቸውን ኢትዮጵያ ላይ በነጻነት ያስፈጽሙ ዘንድ የሚደረግ ማምታቻ ነው!በተረፈ ኢትዮጵያ አንድ ዶ/ር ለ መቶ ሺ ሰው የሆነባት ምስኪን አገር መሆኑዋ እየታወቀ፤ሆንግኮንግ ላይ ቢሮ ከፍቶ እንዲህ ያለ የሮቦት ምርምር ማድረግና በውጤቱም ሶፊያን ሰርተን የሳኡዲ ዜጋ አድርገን ለዓለም ህዝብ አቀረብን ማለት አይናችሁን ጨፍኑና ላሞኛችሁ ከሚል ቁዋንቁዋ ተለይቶ አይታይም።
ለማንኛውም አርብ ሰኔ 22 በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሶፊያን ለመቀበል ከፍ ያለ በጀት ተመድቦ ሽርጉዱ ቀጥሎዋል።ሶፊያም ኢትዮጵያን እንደረገጠች ኢትዮጵያዊ ስም ይወጣላታል።ለጊዜው ሁለት ስም ተዘጋጅተውላታል።1ኛ ጣይቱ፣2ኛ ሉሲ!
ይህ ሁሉ ነገር ምን ማለት ነው???ይህ ጉዳይ ለኢትዮጵያና ለህዝቡዋ ምኑ ነው?ይህ አይነቱ ተግባርና አካሄድስ የቅዱሱ ፈጣሪያችን ዓላማና ፍላጎት ወይስ የክፉው የሳጥናኤል ዓላማና ፍላጎት?ራሳችሁን ጠይቁ!ሌሎች አስተዋይ ዜጎችም እንዲጠይቁ መረጃውን ሼር በማድረግ ተባበሩ።
Read more here
Friday, June 15, 2018
ኢትዮጵያና የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች 3 ቢሊየን ዶላር ድጋፍ ተፈራረሙ
ኢትዮጵያና የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች 3 ቢሊየን ዶላር መጠን ያላቸው የውጭ ምንዛሬ ድጋፍና ኢንቨስትመንት ስምምንቶችን ተፈራረሙ። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ልዑል አልጋወራሽ ሼክ መሀመድ ቢን ዛይድ አል ነኸያን በኢትዮጵያ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ለማድረግ አዲስ አበባ አዲስ አበባ ገብተዋል።
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በመገኘት ለልዑል አልጋወራሽ ሼክ መሀመድ አቀባበል ያደረጉላቸው ሲሆን፥ የቦሌ ለሚ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርክ ግንባታ የሚገኝበትን ደረጃ በጋራ ጎብኝተዋል። በመቀጠልም በብሄራዊ ቤተመንግስት ውይይት አድርገዋል።
በውይይታቸውም ላይ የሀገራቱ የቢዝነስ፣ ኢኮኖሚ እና የህዝብ ለህዝብ ግኑኝነት እንደዚሁም አካባቢያዊ የሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች ተነስተዋል።
ሀገራቱ በተለያዩ ዘርፎች በጋራ መስራት የሚያስችሏቸውንም በአጠቃላይ 3 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር መጠን ያላቸው የውጭ ምንዛሬ ድጋፍ እና ኢንቨስትመንት ስምምነቶችን ማምሻውን ተፈራርመዋል።
ከስምምነታቸው መካከልም ኢትዮጵያ ለተለያዩ የውጭ ምንዛሬ ጥያቄዎች ምላሽ እንደትሰጥ የሚያስችል የ1 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር የውጭ ምንዛሬ ድጋፍ ስምምነት ይገኛል።
ይህም ገንዘብ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ የሚቀመጥ መሆኑም ነው የተገለፀው።
2 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላሩ ደግሞ የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ባለሀብቶች በቀጥታ ኢንቨስትመንት የሚያፈሱት እንደሆነ ተመልክቷል።
ይህም ቀጥታ ኢንቨስትመንት በኢንዱሰትሪ ፓርኮች፣ በማምረቻ ፋብሪካዎች፣ በሆስፒታል፣ በሆቴልና የገበያ ማእከላት ልማት ላይ የሚውል ነው።
ሀገራቱ ኢንቨስትመንትን እና ቱሪዝምን በጋራ ለማስፋፋት እንዲሁም የዲፕሎማቲክ ቪዛን በየራሳቸው ለማስቀረት የተዘጋጁ ስምምነቶችንም ተፈራርመዋል።
ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ መሀመድ ቢን ዛይድ አል ነኸያን በቆይታቸው የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳፋኪ ጋር ይወያያሉ ተብሎም ይጠበቃል።
ከዚህ በተጨማሪም ልዑል አልጋ ወራሹ በኢትዮጵያ በሚኖራቸው የሁለት ቀናት ቆይታ የመስክ ጉብኝትም ያደርጋሉ ነው የተባለው።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በቅርቡ በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ በቆይታቸውም ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ልዑል አልጋ ወራሽ ሼክ መሀመድ ቢን አል ነኸያን ጋር በአቡ ዳቢ ተወያይተዋል።
በዚህም ወቅት ሁለቱ ሀገራት ወዳጅነታቸውን እና ትብብራቸውን የበለጠ ማጠናከር በሚችሉበት ሁኔታ እንዲሁም በወቅታዊ አካባቢያዊ እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ መምከራቸውም ይታወሳል።
Source: Fana
Thursday, June 14, 2018
የኢትዮጵያ አዲሱ የለዉጥ ጉዞ በሲ ኤን ኤን እይታ
የኢትዮጵያ አዲሱ የለዉጥ ጉዞ በሲ ኤን ኤን እይታ። ሲ ኤን ኤን ኢትዮጵያን በሚመከከት ባወጣዉ ሰፋ ያለ ትንታኔ በሀገሪቱ ታሪክ ያልተስተዋለ ፖለቲካዊ ለዉጥ እየተካሄደ መሆኑን አስነብቧል፡፡
በቅርቡ ወደ ስልጣን የመጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ የለዉጡ መሪ ናቸዉም ብሏል፡፡ የወሰዷቸዉ ወሳኝ እርምጃዎች እና ያሳለፏቸዉ ዉሳኔዎች የፖለቲካ ካርታዉን በመቀየር እና የህዝቡን እምነት በማግኘት ረገድ ጉልህ ሚና ተጫዉተዋል፡፡
ሲኤን ኤን በትንታኔዉ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር የዶ/ር አብይ አስተዳደር ካከናወናቸዉ ተግባራት መካከል የፖለቲካ እስረኞችን መፍታቱ፤ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማንሳቱ፤ የአልጀርስ ስምምነትን ለመቀበል መወሰኑ እና በመንግስት ስር ሲተዳደሩ የቆዩ ዘርፎችን ለባለሀብቶች ለማዛወር ማቀዱ ይጠቀሳሉ ይላል፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ ከሹመተ በዓላቸዉ በኋላ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በመዘዋወር የህዝቡን ብሶት አድምጠዋል፡፡ መንግስታቸዉም ዲሞክራሲን ለማስፈን እና ሀገራዊ አንድነትን ለማጠናከር ተጨባጭ እርምጃዎችን እንደሚወስድ ለህዝቡ አረጋግጠዋል ሲል አስፍሯል ትንታኔዉ፡፡
የፖለቲካ እስረኞች መፈታታቸዉ፤ ከተቃዋሚዎች እና ከህዝቡ ጋር የለዉጥ ዉይይቶች መካሄዳቸዉ፤ ከሀገር ለተባረሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እና ግለሰቦች ወደ ሀገራቸዉ እንዲገቡ ጥሪ መቅረቡ፤ እንዲሁም በደህንነት፤ ፍትህ እና ሌሎች ተቋማት የአመራር ለዉጦች መደረጋቸዉ በጎ ጅማሬዎች ናቸዉ ብሏል ትንታኔዉ፡፡
ዶ/ር አብይ አዲስ የታሪክ መክፈታቸዉን እና በህዝቡ የተስፋ ጭላንጭል ማሳደራቸዉንም አስፍሯል፡፡
የኢትዮ ኤርትራ ደም አፋሳሽ ጦርነት በትንታኔዉ ተብራርቷል፡፡ መቶ ሺ የሚገመት ሰዉ የተሰዋበት ጦርነት መንስኤ የድንበር ይገባኛል ጥያቄ መሆኑ በሁለቱ መንግስታት ቢቀርብም የተወሳሰበ ታሪካዊ እና ባህላዊ ስረ-መሰረት እንዳለዉ አሳይቷል፡፡
የኢትዮ-ኤርትራ ወታደረዊ ግጭትን ለማስቆም እና ማህበራዊ ብሎም ኢኮኖሚያዊ ግንኙነታቸውን ለማደስ እ.ኤ.አ በ2000 የአልጀርሱን የሰላም ስምምነት ሀገራቱ ፈርመዋል፡፡ ሆኖም በተለያዩ ምክንያቶች የኢትዮጵያ መንግሰት የስምምነቱን መፈጸም ሳይቀበል ቀርቷል፡፡
የኤርትራ መንግስት ከኢትዮጵያ ጋር ግንኙነቱን ለማሻሻል የአልጀርሱን ስምምነት መቀበል እንደ ቅድመ ሁኔታ ላለፉት 16 አመታት ሲያስቀምጥ ቆይቷል ይላል ትንታኔው፡፡
የዶ/ር አብይ አስተዳደር የአልጀርስ ስምምነትን ለመቀበል መወሰኑ የኤርትራን ጥያቄ የመለሰ ነው፡፡ በዚህም የኤርትራ መንግስት ለ16 አመታት ሲያነሳው የቆየውን ምክንያት ዳግም በቅድመ ሁኔታነት ማቅረብ አይችልም በማለት ትንታኔው ያብራራል፡፡ ውሳኔውም የድንበር ኮሚሽኑን ውሳኔ ያከበረ እና በሁለቱ ሀገራት መካከል ብሎም በቀጠናው ሰላም እና መረጋጋትን ለማስፈን የሚያስችል ነው ይላል የሲኤን ኤን ዘገባ፡፡
በተጨማሪ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከመንግስት ቁጥጥር ነፃ ለማድረግ የተላለፈውን ውሳኔ ተመልክቷል፡፡ ውሳኔው እንደ በረራ፣ ሀይል፣ ቴሌኮም እና ሌሎች ዘርፎችን ሙሉ በሙሉ አልያም በከፊል ለግል ባለሀብቶች ለማዘዋወር ያለመ ነው ሲል ትንታኔውን ያትታል፡፡
እንደ ትንታኔዉ ከ1997ቱ አወዘጋቢ ምርጫ በኋላ የኢህአዴግ መንግስት የልማታዊ ዴሞክራሲ ኢኮኖሚ ጽንሰ ሀሳብን በዋናነት መከተል ጀምሯል፡፡ ባለፉት አስርት አመታት ፈጣን እድገትም አስመዝግቧል፡፡ በዓለማችን ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ካስመዘገቡ ሀገራት ተርታም ኢትዮጵያ ተመድባለች፡፡ ሆኖም የእድገቱን መጠን እና የአህዛዊ የመረጃዎችን ታማኝነት ጥርጣሬ ውስጥ የሚያስገቡ ምክንያቶች ተስተውለዋል፡፡
ለአብነትም ፍትሀዊ ያልሆነ የሀብት ክፍፍል ተጠቃሽ ነው፡፡ ቀደም ሲል በሀገሪቱ ሲተገበር የቆየዉ ልማታዊ ዲሞክራሲ ኢኮኖሚ ርዕዮተ ዓለም ለሙስና እና ለመሬት መሸንሸን የተጋለጠ እንዲሁም አያሌ ዜጎችን ያለ በቂ ካሳ ለመፈናቀላቸዉ መንስዔ መሆኑን ይገልጻል፡፡
የዶ/ር አብይ አስተዳደር መሰል እና ሌሎች ችግሮችን ለመቅረፍ አዲስ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ አካሄድ መከተል መጀመሩን የተላለፉ ዉሳኔዎች ያሳያሉ ሲል ትንታኔዉ ያስረዳል፡፡
ትንታኔዉ በመጨረሻም አዲሱ ኢኮኖሚያዊ አካሄድ ችግሮች ሊገጥሙት አንደሚችሉ እና መንግስት ጥንቃቄ ማድረግ አንዳለበት ጠቁሟል፡፡ ለአብነት እጅግ ትርፋማዉን የበረራ ዘርፍ ለባለሀብቶች ማስተላለፍ የተፈለገበት ምክንያት ግልጽ አለመሆኑን ጠቅሶ ዉሳኔዉ የበረራዉ ዘርፍ ለሀገር የሚያስገኘዉን ገቢ ሊቀንስ ይችላል ነዉ ያለዉ፡፡
የዉጭ ባለሀብቶች ወደ ዘርፎቹ ሲሰማሩ የሀገር ዉስጥ ባለሀብቶች ላይ ተጽዕኖ እንዳያሳድሩ መሠራት አለበት፡፡የህዝቡ እኩል ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እና ሙስናን የመሳሰሉ ችግሮችን ለመቀነስ ጥልቅ የሆነ ጥናት እና ክትትል ያስፈልጋል በማለት ትንታኔዉን ይቋጫል፡፡
በቢኒያም መስፍን
ምንጭ፡- ሲ ኤን ኤን
Wednesday, June 13, 2018
"አሁን ያለው የፌደራሊዝም ሥርዓት የአማራውን ህዝባዊ አንድነት የሚገረስስ ሆኖ ነው ያገኘነው" - BBC
ላለፉት ቀናት የመስራች ጉባዔውን በባህር ዳር ከተማ ሲያከናውን የቆየው የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ፤ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላትን በመምረጥ ተጠናቅቋል። በዚህም መሠረት በባህር ዳር ዩኒቨርስቲ የሚያስተምሩት ዶክተር ደሳለኝ ጫኔን የፓርቲ ፕሬዚዳንት አድርጎ መርጧል።
የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ጉዳዮች ኃላፊ ሆነው የተሾሙት አቶ ክርስቲያን ታደለን በፓርቲው ምስረታ፥ ቀጣይ እርምጃዎች እንዲሁም በተነሱ ትችቶች ዙሪያ ቢቢሲ አነጋግሯቸዋል።
ቢቢሲ- በቅርቡ መስራች ጉባኤያችሁን አካሂዳችኋል፤ ምን ይመስል ነበር?
አቶ ክርስቲያን ታደለ- ስብሰባው ከተጠናቀቀ በኋላ የስራ አስፈጻሚው ቁጭ ብሎ ተወያይቶ ነበር። ምስረታው ከጠበቅነው በላይ እጅግ ስኬታማ ነበር። ምስረታውም ትክክለኛ እንደነበረ አረጋግጦልናል። ይህ ጉዳይ የተወሰኑ አባላት ብቻ ጉዳይ አይደለም፤ በትንሹ ከ40 እስከ 45 ሚሊየን የሚገመተው የሁሉም አማራ ተወላጅ ጉዳይ ነው ብለን ነው የምናምነው።
በሃገራችን ህግ መሰረት አንድ ሃገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲ ሲመሰረት ቢያንስ 1500 አባላት ከአምስት ክልሎች ማስመዝገብ ስለሚጠበቅበት፤ እነሱን ነው ለምርጫ ቦርድ በመስራች አባልነት ያስመዘገብነው።
ቢቢሲ- የአጭር፤መካከለኛ እና የረጅም ጊዜ እቅዶቻችሁ ምንድናቸው?
አቶ ክርስቲያን ታደለ- እንግዲህ ሁሉም ሰው እንደሚከታተለው፤ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሁኔታ በየጊዜው ተለዋዋጭ እና እጅግ ፈጣን፤ ጊዜ የማይሰጥና ሌት ከቀን መስራት የሚጠይቅ ነው ብለን እናምናለን።
የአጭር ጊዜ ግባችን ድርጅቱን ለህዝቡ ማስተዋወቅ ነው። አደረጃጀቱን በከተማ፤ በገጠር እንዲሁም ምሁራን አካባቢ ማጠናከር እናስባለን። በሃገር ውስጥም ከሃገር ውጪም ያለውን የአማራ ተወላጅ እናደራጃለን። ከዚያም ቀጥሎ ሊመጣ የሚችለው፤ እንደ ሃገር በአሁኑ ሰአት በጣም ፈጣን የሚባሉ ውሳኔዎች እየተወሰኑ ስለሆነ፤ አማራውን በቁመቱ እና በወርዱ ሊወክለው የሚችል የፖለቲካ ፓርቲ የለም ብለን እናምናለን።
ከዚህ በኋላ ማንኛውም አማራውን የሚመለከቱ ድርድሮች እና ጉዳዮች ላይ ህዝቡን ወክለን የመካፈል እንዲሁም የአማራውን ዘላቂ ጥቅሞች፤ፍላጎቶች እና መብቶችን ለማስከበር ጥረት እናደርጋለን።
በቀጣይ ደግሞ 2012 ላይ በሚካሄደው ሃገር አቀፍ ምርጫ ላይ እንሳተፋለን። በኛ እምነት የፖለቲካ ስልጣን ላይ ያለው ስርአት፤ አማራው እያጋጠመው ላለው የህልውና አደጋ ዋናው ምንጩ ነው ብለን ነው የምናስበው።
ስለዚህ በምርጫ የፖለቲካ ስልጣን ይዘን ይህንን የተዛባ ግንኙነት የማስተካከል ስራዎችን ለመስራት ነው የምናስበው።
ላፉት ሶስት አስርት አመታት ለሚጠጋ ጊዜ ስርአቱ ከተቀዳበት ህገ መንግስታዊ ድንጋጌው ጀምሮ አማራ ጠል እና ያገለለ እንዲሁም ህልውናውን የሚፈታተን ነው።
የረዥም ጊዜ እቅዳችን እነዚህን የህልውና ጥያቄዎች ማስከበር እና መሰል ተግባራት ወደፊት እንዳይፈጸሙበት የሚያስችል መዋቅራዊ ስርአት መገንባት ነው።
ቢቢሲ- በአጠቃላይ ህዝቡን ከመወከል አንጻር ምን አቋም አላችሁ? ምክንያቱም በስራ አስፈጻሚ ምርጫችሁ ወቅት ለሴቶች ብዙ እድል አልሰጣችሁም በሚል ቅሬታ እና ትችት ተነስቶባችሁ ነበር።
አቶ ክርስቲያን ታደለ- ይህ ቅሬታ በተለያየ መንገድ ለኛም ደርሶናል። በመሰረታዊነት የ13 ስራ አስፈጻሚ አባላት ምርጫ ነው የተደረገው። ከአስራ ሶስቱ ደግሞ አንዷ ብቻ ሴት ናት። ሌላው ደግሞ የሃይማኖት ጉዳይ ነው እየተነሳ የነበረው። መታወቅ ያለበት በመሰረታዊነት የህልውና ጉዳይ መሆኑ ነው።
ስለዚህ ሁሉም የተመረጠው በችሎታ እና በችሎታ ብቻ ነው። መሰረት ያደረግነው እሱን ነው። አንዱ አማራ ሁሉንም አማራ ይወክላል፤ ሁሉም አማራ ለአንዱ አማራ ዘብ ይቆማል በሚለው መርሃችን መሰረት ነው የምንሰራው። ለእያንዳንዱ የስራ ዘርፍ ብቃት ያላቸውን ሰዎች ነው የመለመልነው። የሴቶች ተሳትፎም ቢሆን፤ ከስራ አስፈጻሚዎች መካከል አንዷ ብቻ ሴት ብትሆንም፤ በርካታ ሴት መስራች አባላት እንዳሉን እንዲታወቅልን እንፈልጋለን።
ቢቢሲ- አሁን ኢትዮጰያ ውስጥ ያለው ቋንቋ እና ብሄርን መሰረት ያደረገው ፌደራላዊ ስርአት ዙሪያ ምን አይነት አቋም ነው ያላችሁ? አማራ ክልልን እያስተዳደረ ካለው ፓርቲ ጋር ምን አይነት ግንኙነት እንዲኖራቹ ትጠብቃላችሁ?
አቶ ክርስቲያን ታደለ- የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ በመሰረታዊነት ፌደራላዊ ስርአትን አይቃወምም። ይህ ማለት ግን የአማራ ህዝብ ህልውና አደጋ ላይ የሚጥል ፌደራሊዝም ይደግፋል ማለት አይደለም። ለአብነት አሁን ያለው የፌደራሊዝም ስርአት የአማራውን ህዝባዊ አንድነት የሚገረስስ ሆኖ ነው ያገኘነው።
በዋነኛነት የመታገያ ጥያቄያችን የአማራን ህዝብ እንደ ህዝብ አንድነቱን እና የታሪካዊ ግዛት መብቶቹ እንዳይገረሰሱ እና እንዲጠበቅ ማድረግ ነው።
Recent Articles
Recent Video Uploads
Subscribe Ethiopia Today Videos and Watch on You Tube
Ethiopia Today
- Active a minute ago with many
- videos
