Monday, October 17, 2016

ኢትዮጵያን ከግብፅ ጋር ዳግም እሰጥ አገባ ውስጥ የከተታት ክስተት

የአዲስ አበባና የዙሪያዋ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላንን በመቃወም በ2007 ዓ.ም. በኦሮሚያ ከተሞችና ዩኒቨርሲቲዎች የተጀመረው ተቃውሞ ለተወሰኑ ወራት የተረጋጋ ቢመስልም በ2008 ዓ.ም. በኅዳር ወር ተቀስቅሷል፡፡
በኦሮሚያ ዳግም ላገረሸው ተቃውሞ በምዕራብ ኦሮሚያ ጊንጪ ከተማ የሚገኝ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ይዞታ በከፊል ለባለሀብት መሸጡን በመቃወም ተማሪዎቹ ያነሱት ተቃውሞ መነሻ ምክንያት መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ መነሻው ይህ ቢሆንም፣ የአዲስ አበባና የዙሪያው ኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን ላይ የነበረው ተቃውሞ በርካታ አካባቢዎችን ያደረሰ ግጭት አዘል ተቃውሞ መቀስቀሱ ይታወቃል፡፡
በዚህም የበርካታ ሰዎች ሕይወት አልፏል፡፡ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል በተመሳሳይ ወቅት የተነሳው ግጭት ከቅማንት ብሔረሰብ ማንነት ጋር የተያያዘ እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ የቅማንት ብሔረሰብ ማንነትን የክልሉ መንግሥት ዕውቅና ሊሰጥ አልቻለም በሚል መነሻ የተቀሰቀሰው ግጭት የበርካቶች ሕይወት ቀጥፏል፡፡ ንብረቶች ወድመዋል፡፡ አንድ ብሔር ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች ተሰንዝረዋል፡፡
በሰሜን ጐንደር ከቅማንት ጋር ተያይዞ የተነሳው ግጭት በፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ ካገኘ በኋላ መረጋጋትን አሳይቷል፡፡ ይሁን እንጂ በዚያው በሰሜን ጎንደር ዞን ከወልቃይት ማንነትና የወሰን ለውጥ ጥያቄ ጋር የተያያዘ ጥያቄ ተቀስቅሷል፡፡
በትግራይ ክልል ውስጥ የተካለለው የወልቃይት ፀገዴ ሕዝብ አማራ ነው መተዳደር ያለበትም በአማራ ክልል ውስጥ ነው በሚል የተነሳው ጥያቄ ይዘቱን ቀይሮ፣ በአማራ ክልል በጎንደርና በጐጃም ዞኖች በመንግሥት ላይ ጥያቄ የሚያነሱ ሠልፎችና አድማዎች፣ እንዲሁም ባህሪው ተቀይሮ ወደ ንብረት ማውደም ተቀይሯል፡፡
በእነዚህ ሁለት የአገሪቱ አካባቢዎች የተነሳው የፖለቲካ ቀውሶች በማኅበራዊ ሚዲያ እየተመሩ በርካታ አካባቢዎችን ከማዳረሳቸውም በላይ የጋራ ዓላማ ያላቸው መስለዋል፡፡
መንግሥት በተደጋጋሚ ጊዜ ስለተነሱበት ጥያቄዎች ራሱን ተጠያቂ ሲያደርግ መቆየቱ ይታወቃል፡፡
ባለፈው ሳምንት ሰኞ የተወካዮች ምክር ቤትንና የፌዴሬሽን ምክር ቤትን የጋራ ጉባዔ በንግግር የከፈቱት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ተሾመ ሙላቱ በአብዛኛው ያነሱትም፣ መንግሥት ሊመልሳቸው የሚገቡ ጥያቄዎች በፍጥነት ባለመመለሳቸውና ከፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል፣ ኢኮኖሚያዊ ጥቅምን ከግምት ያላከተተ የካሳ ክፍያ በመክፈል አርሶ አደሩን ከመሬቱ ማፈናቀል፣ እንዲሁም የማንነት ጥያቄዎችን በአግባቡ አለመመለስ መሠረታዊ የኅብረተሰቡ ጥያቄዎች መሆናቸውን ነው፡፡ ይሁን እንጂ ይህ ጥያቄ በአግባቡ መመለስ ባለመቻሉ በተለያዩ የውጭ ኃይሎችና በጽንፈኛ የኢትዮጵያ ዳያስፖራዎች መጠለፉን ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ ቀን ለውጭ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ መግለጫ የሰጡት የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ኢትዮጵያውያን ፍትሐዊ ጥያቄዎችን ቢያነሱም የግብፅ መንግሥት ተቋማትና የኤርትራ መንግሥት ይህንን የሕዝብ ጥያቄ ለራሳቸው ዓላማ በመጥለፍ ኢትዮጵያን ለመበታተን ሲያጠነጥኑ፣ በገንዘብ ሲደግፉና ሲያስታጥቁ እንደተደረሰባቸው ለዚህም የኢትዮጵያ መንግሥት አሳማኝ ማስረጃ እንዳለው ገልጸዋል፡፡
ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ በንግግራቸው፣ ‹‹በቅርቡ በአንዳንድ የአገራችን ክልሎች ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመናድ ሲካሄዱ የቆዩ አፍራሽ እንቅስቃሴዎችን መሠረታዊ ባህርይና አንድምታ በትክክል መገንዘብ ተገቢ ነው፤›› በማለት፣ የአገሪቱ ሕዝቦች በሰላማዊ መንገድ ያቀረቡት ቅሬታን በመጥለፍ ወደ ሁከትና አውዳሚ እንቅስቃሴ ለመቀየር የተረባረቡ የውጭ ኃይሎች መኖራቸውን ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ በትንሳኤ ላይ መሆኗን የማይቀበሉ አገሮችና ‹‹የኒዮሊብራል›› አጀንዳቸውን ለመጫን የሚፈልጉ ኃይሎች ኢትዮጵያን ለማተራመስ በስፋት እየተንቀሳቀሱ መሆኑን፣ ፕሬዚዳንቱ ለሁለቱ ምክር ቤቶች ባደረጉት ንግግር ጠቁመዋል፡፡
‹‹ከጽንፈኛ ዳያስፖራዎች ጀምሮ በአባይ ወንዛችን ላይ የተጠቃሚነት መብታችንን ለማረጋገጥ የጀመርነውን እንቅስቃሴ ለማኮላሸት የሚንቀሳቀሱት እነዚህ ወገኖች፣ በቅርቡ ታላቁን የኢሬቻ በዓል ከማወክ ጀምሮ በልዩ ልዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች ያካሄዱት ውድመትና ቃጠሎ በማንኛውም ሚዛን ፍትሐዊነት የሌለው ነው፡፡ በመሆኑም መንግሥት ይህን የመሰለው አፍራሽና ከባድ የውጭ ጣልቃ ገብነትን ታዝሎ የመጣ ፀረ ኢትዮጵያ እንቅስቃሴ እንዲመከትና ወንጀለኞቹም በጥብቅ በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ ያደርጋል፡፡ በቃጠሎ የወደሙ ንብረቶች በተለይ ደግሞ የምርት ተቋማት አገራችንና ሕዝቦቿ ከውጭ የልማት አጋሮቻችን ጋር በመተባበር በአፋጣኝ መልሰው እንዲገነቡና ለላቀ ምርታማነት እንዲበቁ ጠንካራ ርብርብ ይደረጋል፡፡ በመሆኑም መላ የአገራችን ሕዝቦች ኢትዮጵያን እንደፈራረሱት የሰሜን አፍሪካና የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ለማተራመስ የሚደረገውን ይህን አፍራሽና አሳፋሪ ሙከራ መንግሥትና ሕዝብ በጀመሩት መንገድ በጋራ ይፋለሙታል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹በተለይ ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የማንንም እጅ ሳንጠብቅ በመላ የአገሪቱ ሕዝቦች ተሳትፎና በአገራዊ አቅም በመተማመን መገንባት መጀመራችን ያስቆጣቸው አገሮች፣ ረዘም ላሉ ዓመታት ውስጥ ውስጡን ሲዘጋጁ ከርመው በአሁኑ ጊዜ ጽንፈኛ የዳያስፖራ ኃይሎች ከቀሰቀሱት ነውጥ ጋር በመመጋገብ አገሪቱን ለማተራመስ በቀጥታ እየተረባረቡ ይገኛሉ፤›› ብለዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ እንደተናገሩት በቀላሉ ሊነሱ የሚችሉ ወጣቶችን የጥፋት ሐሳብ፣ ክብሪትና ነዳጅ እያስታጠቁ ለአገሪቱ ቁልፍ የኢኮኖሚ አስተዋጽኦ ያላቸውን ፋብሪካዎች፣ የአበባ እርሻዎችና ሌሎች ተቋማት በማጋየት ከፍተኛ ውድመት እንዳስከተሉ ተናግረዋል፡፡
‹‹የኦነግና የግንቦት ሰባት መሪዎች ከግብፅ መንግሥት ተቋማት ጋር እጅና ጓንት በመሆን ባቀነባበሩት የጥፋት እንቅስቃሴ በርካታ አገራዊና የውጭ ባለሀብቶችና ሠራተኞቻቸውን ለአደጋ ያጋለጠ የታሰበበት ከፍተኛ ውድመት ፈጽመዋል፤›› ብለዋል፡፡
ይህንን ተከትሎ የፌዴራል ፖሊስ ከኦነግ ጋር ግንኙነት በመፍጠርና አመራር በመቀበል የጥፋት ተግባር ተሰማርተዋል በሚል የጠረጠራቸውን 17 ወጣቶች በቁጥጥር ሥር አውሎ ሰሞኑን ክስ መሥርቶባቸዋል፡፡
እነዚህ ወጣቶች ከኦነግ አመራሮችና የሽብር ቡድን አባላት ጋር የስልክ ግንኙነት በማድረግ በአገር ውስጥ አባላትን ሲመለምሉ እንደነበር፣ ዓላማቸውም የኢትዮጵያን መንግሥት በኃይል የመለወጥ የፖለቲካ ዓላማ እንደነበራቸው በክሱ ገልጿል፡፡
እነዚህ ወጣቶች መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ፣ በቢሾፍቱ፣ በጅግጅጋና በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞች በማድረግ ሲንቀሳቀሱ እንደነበር የክስ መዝገቡ ያስረዳል፡፡
በምዕራብ ሸዋ ዞን የዕርዳታ እህል የጫኑ ተሽከርካሪዎችን ያቃጠሉ፣ በመንገድ ሥራ ላይ የነበሩ ማሽነሪዎች፣ ሆቴሎችና የአስተዳደር ጽሕፈት ቤቶች ላይ ጉዳት ያደረሱ ተጠርጣሪዎች በነዋሪዎች ጥቆማ በፖሊስ እየተያዙ መሆናቸውን የዞኑ ፖሊስ መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር ደረጀ ሙላት ተናግረዋል፡፡
በአርሲ ነገሌ የውኃ ፕሮጀክቶች ላይ ጉዳት ያደረሱና የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎችን ያቃጠሉ በርከት ያሉ ወጣቶች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የዞኑ መስተዳደር አካላት ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ታማኝ ማስረጃ እንዳላቸው በመግለጽ የግብፅ ተቋማትን እየወነጀሉ ሲሆን፣ የግብፅ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ መንግሥታቸው በኢትዮጵያ ውስጥ በተፈጠረው ግጭትና አለመረጋጋት እጁ እንደሌለበት በመግለጽ እያስተባበሉ ይገኛሉ፡፡
የግብፅ ፕሬዚዳንት ለአገራቸው የመከላከያ ሠራዊት ባደረጉት ንግግር፣ ‹‹ግብፅ ከማንም አገር ጀርባ አታሴርም፤›› ማለታቸውን የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡
‹‹ለኢትዮጵያውያን ወንድሞቼ ማረጋገጥ የምፈልገው ግብፅ ምንም ዓይነት ድጋፍ ለኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች አላደረገችም፡፡ መቼም አታደርግም፤›› ማለታቸውም ተሰምቷል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይህንን ይበሉ እንጂ የግብፅ መንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተለያዩ ጊዜያት ከቀጣናቸው በመውጣት አለመረጋጋት የሚታይባቸውን የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች በድብቅ በመጎብኘት የፖለቲካ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ታይተዋል፡፡
ከእነዚህም አገሮች መካከል ኤርትራ አንዷ ስትሆን በዚህች አገር የግብፅ ፍላጐት እንደተሟላ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
የኤርትራ መንግሥት የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎችን በማስጠለል ሲተባበር፣ ግብፅ አስፈላጊውን የገንዘብ ድጋፍ እያደረገች መሆኑን መንግሥት ይገልጻል፡፡
ይህንኑ ተመሳሳይ እንቅስቃሴ በሶማሌላንድና በደቡብ ሱዳን ለመድገም እንቅስቃሴ የተደረገ ቢሆንም፣ የሶማሌላንድ መንግሥት አለመቀበሉን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
በሶማሌላንድ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች መድረክ ዋና ዳይሬክተር ሞሐመድ አህመድ ባርዋኒ፣ የግብፅ መንግሥት ኃላፊዎች ከጥቂት ወራት በፊት በሶማሌላንድ ያደረጉት ጉብኝት ዓላማው፣ በአገሪቱ ጦራቸውን ለማስፈር የሚያስችላቸውን ስምምነት ለመፍጠር ቢሆንም አልተሳካላቸውም የሚል ምላሻቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ዓላማቸውን እውን ለማድረግ ከየመን ጋር የተያያዙ ምክንያቶችን ያቅርቡ እንጂ፣ ጉዳያቸው ኢትዮጵያ ነች የሚል እምነት እንዳላቸው ባርዋኒ ተናግረዋል፡፡
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የደቡብ ሱዳንን ችግር እንዲፈታ ኃላፊነት የሰጠው ለምሥራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግሥታት (IGAD) ቢሆንም፣ ግብፅ በዚህ አካባቢ ጦሯን ለማሰማራት ከፍተኛ ፍላጐት እንዳላት እየገለጸች ትገኛለች፡፡ በግብፅ ለረጅም ዓመታት ግብፅ የቆዩ አንድ ኢትዮጵያዊ ዲፕሎማት እንደገለጹት ከሆነ ደግሞ የግብፅ መንግሥት ሁለት እጆች እንዳሉት ይናገራሉ፡፡
አንደኛው ውስጥ ለውስጥ የሚንቀሳቀስበት ከመንግሥት ጋር ንክኪ የሌላቸው ተደርገው የሚቆጠሩ ተቋማት፣ ነገር ግን ሙሉ የበጀት ድጋፍ በግብፅ መንግሥት የሚደረግላቸው መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ ሌላው ግን ራሱ የግብፅ መንግሥት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የሚፈጽመው ሴራ ነው፡፡
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሸን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ባለፈው ዓርብ ባወጣው መግለጫ፣ ባለፉት ዓመታት አገሪቱ ያስመዘገበችውን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ለማደናቀፍ፣ የወጣቶችን ሕጋዊ የተጠቃሚነት ጥያቄ ጠልፈው መሠረተ ልማቶችን ወደ ማውደም የተሸጋገሩ ኃይሎች ተልዕኮ፣ ወደ ድህነት የተመለሰችና የፈራረሰች አገር መፍጠር ነው ብሏል፡፡
በአገር ውስጥና በውጭ አገሮች ለዚሁ ዓላማ የተደራጁና በኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች የሚደገፉ የሁከት ኃይሎች የሞከሩት ይህንኑ ነበር ያለው መግለጫው፣ እነዚህ ኃይሎች በተቀናጀ መንገድ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱንና የሕዝብ ደኅንነትን አደጋ ላይ ለመጣል ተንቀሳቅሰዋል በማለት አክሏል፡፡ Read more here

No comments:

Post a Comment

Related Posts Plugin for WordPress, Blogger...

Recent Articles

Recent Video Uploads

Subscribe Ethiopia Today Videos and Watch on You Tube

Ethiopia Today

  • Active a minute ago with many
  •  
  •  videos
Ethiopia Today bringing you recent information about Ethiopia. It bring you, news, Amharic movies,  Musics and many clips. subscribe and get many Videos on time