Monday, June 17, 2024

ከውጭ በተላከ ገንዘብ ሀብት አፍርቶ የተላከበትን ደረሰኝ ያላቀረበ ንብረቱ እንዲወረስ የሚደነግግ አዋጅ ቀረበ!

 

  • በጥፋተኝነት ላይ ያልተመሠረተ ንብረት የመውረስ ድንጋጌም በአዋጁ ተካቷል
  • አዋጁ የሚፀድቅ ከሆነ 10 ዓመት ወደኃላ ተመልሶ ተፈጻሚ ይሆናል

ከውጭ በተላከ ገንዘብ ሀብት አፍርቶ የተላከበትን ደረሰኝ ያላቀረበ ሰው ወይም ሊታወቅ ከሚችል ገቢው በላይ ሀብት አፍርቶ ምንጩ ሕጋዊ መሆኑን ማረጋገጥ ያልቻለ ሰው፣ ንብረት በመንግሥት እንዲወረስ የሚፈቅድ ድንጋጌ የያዘ ረቂቅ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀረበ።

Ethiopia's remittances inflow in danger 

ረቂቅ አዋጁ ‹‹የንብረት ማስመለስ አዋጅ›› የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን፣ ባለፈው ማክሰኞ ሰኔ 4 ቀን 2016 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ የመጀመሪያ ንባብ ተካሂዶበታል።

የረቂቁ ስያሜ ‹‹የንብረት ማስመለስ አዋጅ›› እንዲሆን የተመረጠበት ምክንያት ወንጀል የሚለው ቃል ከገባ ምንጩ ያልታወቀ ሀብትን፣ እንዲሁም ወንጀልን ማቋቋም አስፈላጊ ሳይሆን ሲቀርና በወንጀል ኃላፊነት የማይረጋገጡ ንብረቶች በሚኖሩበት ወቅት ንብረቶችን ለማስመለስ አያስችልም ተብሎ በመታመኑ እንደሆነ ረቂቅ አዋጁን ለማብራራት የቀረበው አባሪ ሰነድ ያስረዳል።

የረቂቅ አዋጁ ድንጋጌዎችና አባሪ የተደረገው ማብራሪያ ሰነድ እንደሚያስረዱትም፣ መንግሥት ንብረትን ለማስመለስ ሲል በሦስት ዋና ዋና መንገዶች ንብረቶችን ሊወርስ ይችላል። እነዚህም መንገዶች፣ ‹‹ምንጩ ያልታወቀ ንብረት መውረስ››፣ ‹‹በጥፋተኝነት ላይ ያልተመሠረተ መውረስ›› እና ‹‹በጥፋተኝነት ላይ የተመሠረተ›› መውረስ ናቸው።

በረቂቅ አዋጁ ድንጋጌ መሠረት፣ ማንኛውም ሰው ምንጩ ያልታወቀ ንብረት አፍርቷል ተብሎ ንብረቱ ሊወረስ የሚችለው፣ ግለሰቡ ያለው ንብረት ወይም የኑሮ ደረጃው አሁን ባለበት ወይም አስቀድሞ በነበረበት ሥራ ወይም በሌላ መንገድ ከሚያገኘው ወይም ሲያገኝ ከነበረው ሕጋዊ ገቢ ጋር የማይመጣጠን ሲሆንና የንብረቱን ወይም የኑሮ ደረጃውን ምንጭ በተመለከተ ምክንያታዊ የሆነ የወንጀል ጥርጣሬ ሲኖር ነው። 

ይህ ሁኔታ መኖሩ ሲታወቅ ወይም ዓቃቤ ሕግ ምክንያታዊ ጥርጣሬ ሲኖረው የፍትሐ ብሔር ክስ መመሥረት የሚችል ሲሆን፣ ክሱ የቀረበበት ሰው ንብረቱ ወይም የኑሮ ደረጃው በሕጋዊ መንገድ የተገኘ መሆኑን ጉዳዩን ለሚመለከተው ፍርድ ቤት አስረድቶ ማረጋገጥ እንደሚኖርበት ረቂቅ አዋጁ ድንጋጌ ያመለክታል። 

ይህም ማለት ምንጩ ያልታወቀ ንብረት መኖሩን ለፍርድ ቤት የማስረዳት ወይም የማረጋጥ ሸክም የከሳሽ ዓቃቢ ሕግ ሳይሆን ምንጩ ያልታወቀ ንብረት አለው ተብሎ የተጠረጠረው ግለሰብ ወይም ሕጋዊ ሰው እንደሚሆን የረቂቅ አዋጁ ድንጋጌዎች ያመለክታሉ።

ረቂቅ አዋጁን ለማብራራት የቀረበው አባሪ ሰነድም ንብረት ማስመለስና መውረስ የሚችልባቸውን ሁኔታዎች የሚዘረዝሩ አንቀጾችን ይዟል። በዚህም መሠረት ምንጩ ያልታወቀ ንብረት የሚወረስበትን ሁኔታ አስመልክቶ የሚከተለውን ማብራሪያ አስቀምጧል።

‹‹ምንጩ ያልታወቀ ንብረት አፍርቷል ተብሎ የተጠረጠረ ሰው፣ ንብረቱን ያፈራው ከውጪ በተላከለት ገንዘብ ነው የሚል ከሆነ፣ ግለሰቡ ገንዘቡ በሕጋዊ መንገድ በባንክ ሥርዓት ውስጥ ያለፉ ግብይቶች ወይም ክፍያዎች ስለመሆናቸው በተገቢው የባንክ ደረሰኝ  አስደግፎ ማቅረብ የሚገባው ሲሆን፣ ከዚህ ውጪ ያለው ግን እንደ ምንጩ ያልታወቀ ገቢ ተደርጎ የሚቆጠርና የሚወረስ ይሆናል››።

ምንጩ ያልታወቀ ንብረት ክስ በሚቀርብበት ጊዜና የንብረቱ የገንዘብ መጠን በአዋጁ አንቀጽ 8 ላይ የተደነገገ ሲሆን፣ ክስ የሚቀርብበት ጊዜን አስመልክቶም አዋጁ ከሚፀድቅበት ጊዜ አንስቶ ወደ ኃላ 10 ዓመት ተመልሶ ተፈጻሚ እንደሚሆን ረቂቅ አዋጁ ይጠቅሳል። 

አዋጁ ወደኋላ 10 ዓመት ተመልሶ ተፈጻሚ በሚሆንበት ወቅት ምንጩ ያልታወቀ ንብረትን ለመክሰስ መሠረት የሚሆነው ዝቅተኛ የገንዘብ መጠን አምስት ሚሊዮን ብር ሲሆን፣ አዋጁ ሥራ ላይ ከዋለ በኋላ ምንጩ ያልታወቀ ንብረት ተጠያቂነት ያለ ምንም የገንዘብ መጠን ተፈጻሚ እንደሚደረግ የረቂቅ አዋጁ ድንጋጌዎች ያመለክታሉ።

ምንጩ ያልታወቀ ንብረት አፍርቷል ተብሎ በዓቃቤ ሕግ የተጠረጠረ ማንኛውም ሰው የንብረቱን ምንጭ እንዲያስረዳ በዓቃቤ ሕግ የጽሑፍ ጥያቄ እንደሚቀርብለት የሚገልጸው ረቂቅ አዋጁ፣ ይህ ጥያቄ የደረሰው ማንኛውም ሰው ያለውን ማንኛውንም የንብረት ዝርዝርና የተገኘበትን አግባብ የሚያሳይ መግለጫና ዝርዝር ማስረጃዎችን በማያያዝ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ በጽሑፍ ለዓቃቤ ሕግ ማቅረብ እንዳለበት ያመለክታል።

የንብረቱን ምንጭ እንዲያስረዳ የተጠየቀው ሰው የንብረቱን ምንጭ ለማስረዳት የሚያቀርበው ማስረጃ ሕጋዊ መሆን እንዳለበትም ተደንግጓል።

ማስረጃዎችን ለማቅረብ የተመለከተው የአንድ ወር የጊዜ ገደብ አስገዳጅ ሁኔታ ሲኖር ለዓቃቤ ሕግ በሚቀርብ አቤቱታ ሊራዘም እንደሚችል፣ ሆኖም የጊዜ ገደቡ ከስድስት ወራት በላይ እንደማይበልጥ ሪቂቁ ያመለክታል።

ምንጩ ያልታወቀ ንብረት ከሚወረስባቸው መንገዶች በተጨማሪ ‹‹በጥፋተኝነት ላይ ያልተመሠረተ›› የንብረት መውረስ የሚፈጸምባቸው ድንጋጌዎችም በረቂቅ አዋጁ ተካተዋል። ረቂቅ አዋጁ በሰጠው ትርጓሜ መሠረት ‹‹በጥፋተኝነት ላይ ያልተመሠረተ መውረስ›› ማለት በማንኛውም ዓይነት ወንጀል በፍርድ ቤት ውሳኔ ጥፋተኛ ባይባልም፣ በረቂቅ አዋጁ በተቀመጡ ድንጋጌዎች መሠረት የሚከናወን የንብረት መውረስ ነው።

በዚህም መሠረት በወንጀል ክስ የጥፋተኝነት ውሳኔ ባይሰጥበትም ከወንጀል ድርጊቱ የንብረት ጥቅም አግኝቷል ተብሎ የተጠረጠረ ማንኛውም ሰው ላይ ዓቃቤ ሕግ የንብረት መውረስ ማመልከቻ ለፍርድ ቤት ሊያቀርብበት እንደሚችል ረቂቅ ድንጋጌው ያመለክታል።

በጥፋተኝነት ላይ ያልተመሠረተ የንብረት መውረስ ማመልከቻ ሊቀርብ የሚችልባቸው ሁኔታዎች በረቂቅ አዋጁ የተዘረዘሩ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል አንዱ በወንጀል ድርጊት የተጠረጠረው ወይም የተከሰሰው ሰው ሲሞት፣ ሲያመልጥና ሲጠፋ ወይም ወንጀል ፈጻሚው ሳይታወቅ ሲቀር ነው።

እንዲሁም በይርጋ ምክንያት የወንጀል ጥፋተኝነት ውሳኔ ማሰጠት ሳይቻል ሲቀር፣ የተገኘው ማስረጃ በወንጀል ክስ የጥፋተኝነት ውሳኔ ለማሰጠት የሚያስችል የማስረጃ ምዘና መሥፈርትን የማያሟላ ከሆነ፣ ከወንጀል ድርጊቱ ጥቅም ስለመገኘቱ ምክንያታዊ ጥርጣሬ ሲኖር፣ ተከሳሹ ምሕረት ሲደረግለት፣ የቀረበበት ክስ በማንኛውም ምክንያት ሲቋረጥ፣ ተጠርጣሪው በወንጀል ያለ መከሰስ መብት ያለው እንደሆነ በጥፋተኝነት ላይ ያልተመሠረተ የንብረት መውረስ ክስ ሊቀርብ ይችላል።

በተጨማሪም የጥፋተኝነት ውሳኔ ከተሰጠበት የወንጀል ድርጊት ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚገናኝና በሦስተኛ ወገን ይዞታ ወይም ባለቤትነት ሥር የሚገኝ ንብረት ሲሆን፣ በጥፋተኝነት ላይ ያልተመሠረተ የንብረት መውረስ ክስ ሊቀርብ እንደሚችል ረቂቅ አዋጁ ያመለክታል።

የወንጀል ቅጣቱ በይቅርታ ወይም በምሕረት ቀሪ የተደረገለት፣ የተገደበለት ወይም በአመክሮ የተለቀቀ ማንኛውም ሰው፣ ይህንን ሁኔታ ከወንጀል ድርጊቱ የተገኘውን ንብረት ለመውረስ ለሚቀርብበት ክስ መቃወሚያ አድርጎ ማቅረብ እንደማይችልም ረቂቁ ያመለክታል።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በዚህ ረቂቅ አዋጅ ላይ ባለፈው ማክሰኞ የመጀመሪያ ንባብ (ውይይት) ባካሄደበት ወቅት ሁለት የምክር ቤት አባላት ብቻ አስተያየት የሰጡ ሲሆን፣ አንደኛው አስተያየት ረቂቅ አዋጁ በፍጥነት ፀድቆ ሥራ ላይ እንዲውል የሚጠይቅ ነው። 

ይሁን እንጂ ረቂቅ አዋጁን ለዝርዝር ዕይታ እንዲመራ ድምፅ በተሰጠበት ወቅት ሁለት የምክር ቤት አባላት የተቃውሞ ድምፅ ሰጥተው ረቂቁ በዝርዝር እንዲታይ ለሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተመርቷል።

Read More: https://www.ethiopianreporter.com/130508/

No comments:

Post a Comment

Related Posts Plugin for WordPress, Blogger...

Recent Articles

Recent Video Uploads

Subscribe Ethiopia Today Videos and Watch on You Tube

Ethiopia Today

  • Active a minute ago with many
  •  
  •  videos
Ethiopia Today bringing you recent information about Ethiopia. It bring you, news, Amharic movies,  Musics and many clips. subscribe and get many Videos on time